+251118132191
contact@mint.gov.et
ዲጂታል የአሰራር ሥርዓት በማስፋትና ብቁ የሰው ኃይል በማፍራት ረገድ የተሻለ ስራ መከናወኑ ተመላከተ
አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 5፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ዲጂታል የአሰራር ሥርዓት በማስፋትና ብቁ የሰው ኃይል በማፍራት ረገድ የተሻለ ስራ መከናወኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ።
በለጠ ሞላ (ዶ/ር) የሦስተኛው ሩብ ዓመት የ100 ቀን የዘርፎች አፈጻጸም እና የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ትግበራ ያለፉት ዘጠኝ ወራት አፈጻጸም አሰመልከቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው÷ ዲጂታላይዜሽን ማስፋፋት፣ መሠረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ማድረግ፣ የዘመነ የአሰራር ሥርዓትን መዘርጋት፣ ከሥራ ፈጠራ ጋር በተያያዘ ኢኖቬሽንን ማስፋፋት የሚኒስቴሩ ተልዕኮዎች መካከል መሆናቸውን አንስተዋል።
በዚህም ከግል ዘርፍ ጋር በመተባበር ሰፊ ሥራዎች እየተሰሩ መቆየታቸውን ገልጸው÷ በዲጂታል ዘርፍ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆናቸውን አመላክተዋል።
ቴሌብርን ጨምሮ በዲጂታል መንገድ እየተካሄደ ባለው የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ባለፉት 9 ወራት ወደ 800 ቢሊየን ብር የሚጠጋ ገንዘብ መንቀሳቀስ መቻሉን አንስተዋል።
ይህም ትልቅ እመርታ መሆኑን ገልጸው÷ የጂጂታል ሥርዓት በመዘርጋት ገንዘብ ለማሳተም የሚጠይቀውን ሰፊ ወጪ ለማስቀረት መቻሉን ተናግረዋል።
በሰው ሀብት ልማትም የ5 ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼትቭ ከባለፈው ሐምሌ ወር ጀምሮ ወደ 688 ሺህ ኢትዮጵያዊያን ተመዝግበው ሥልጠና እየወሰዱ መሆናቸውን ገልጸው÷ ከዚህም ውስጥ 270 ሺህ ኢትዮጵያዊያን ሥልጠናውን አጠናቀው ዓለም አቀፍ ሰርቲፊኬት ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።
ይህም የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ እውን ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው በለጠ (ዶ/ር) አስረድተዋል።
በዘርፉ የበለጠ ውጤታማ ለመሆን አዳዲስ ሀገራዊ ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል።
በብዛት የተጎበኙ
መንግስት የቀድሞው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርን በማዋሃድ በ2011 ዓ.ም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ተቋቋመ፡፡
የትኩረት መስኮች
- ምርምር
- ኢኖቬሽን
- የቴክኖሎጂ ሽግግር
- ዲጂታላይዜሽን
ያግኙን
- ስልክ: +251118132191
- ኢሜል: contact@mint.gov.et
- ድረ-ገጽ: www.mint.gov.et
የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገጾች