+251118132191
contact@mint.gov.et
ኢትዮጵያ እና ጣሊያን በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና ፈጠራ ላይ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መከሩ።
የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር በለጠ ሞላ ከጣሊያን የከፍተኛ ትምህርትና ምርምር ሚኒስትር አና ማሪያ በርኒኒ (H.E Ana Maria Bernini) ጋር የኢትዮጵያን ዲጂታል ለውጥ እና በፈጠራ ላይ የተመሰረተ የኢኮኖሚ እድገትን በማጠናከር ላይ ያተኮረ ውይይት አድርገዋል።
በውይይቱ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር በለጠ ሞላ የጣሊያን መንግስት ኢትዮጵያ ጠንካራ ዲጂታል ኢኮኖሚ ለማምጣት እና የቴክኖሎጂ ፈጠራን ለማጎልበት ለምታደርገው ጥረት የ585 ሚሊዮን ብር ድጋፍ መስጠቱን አመስግነዋል።
ሚኒስትሩ ይህ አጋርነት የኢትዮጵያን ዲጂታል መሠረተ ልማት ለማዘመን፣ ልማትን ለማስፋፋት እና በቴክኖሎጂው ዘርፍ የሰው ሀብት አቅም ግንባታ ስራን ለመስራት የታቀዱ የተለያዩ ውጥኖችን ያግዛል ብለዋል።
ዶ/ር በለጠ ሞላ በንግግራቸው የኢትዮጵያን የቴክኖሎጂና ፈጠራ ተግዳሮቶችን ለመፍታት እና ቴክኖሎጂን ለዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገት በማዋል ረገድ ምቹ ስነምህዳርን ለመፍጠር የትብብር አስፈላጊነት ወሳኝ ነው ብለዋል።
በውይይቱ ላይ የጣሊያን የከፍተኛ ትምህርትና ምርምር ሚኒስትር አና ማሪያ በርኒኒ ጣሊያን ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኗን ገልፀው የዲጂታል ፈጠራ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማምጣት ያለውን የለውጥ አቅም አጽንኦት ሰጥተዋል።
በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ፣ በባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ፣ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፣ በኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ፣ በኒኩለር ሳይንስ እና በምርምር ዘርፍ ጣሊያን በትኩረት እየሰራች መሆኑን ጠቅሰው የሁለትዮሽ ግንኙነትን ማጠናከር እንደሚገባም አንስተዋል።
ሁለቱ ሚኒስትሮች በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን አጋርነት የበለጠ ለማጠናከር ያለመ የትምህርት ልውውጥ መርሃ ግብሮችን እና የጋራ የምርምር ስራዎችን ጨምሮ የወደፊት የትብብር መስኮች ላይም መክረዋል።
በብዛት የተጎበኙ
መንግስት የቀድሞው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርን በማዋሃድ በ2011 ዓ.ም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ተቋቋመ፡፡
የትኩረት መስኮች
- ምርምር
- ኢኖቬሽን
- የቴክኖሎጂ ሽግግር
- ዲጂታላይዜሽን
ያግኙን
- ስልክ: +251118132191
- ኢሜል: contact@mint.gov.et
- ድረ-ገጽ: www.mint.gov.et
የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገጾች